በአፋር ሰመራ እንዲደደግ በጥቅምት 30 ቀነ ቀጠሮ ተይዞለት የነበረው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጠቅላላ ጉባኤ ወደ ሀገሪቱ ዋና ከተማ አዲስ አበባ ስለመዛወሩ እየተሰማ ይገኛል፡፡ ላላፉት 4 አመታት እግር ኳሱን ያስተዳደሩት አካላት የመጨረሻ ዘመናቸው በሆነው በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲሁም ምርጫ መካሄድ በፊትም ከወዲሁ በርከት ያሉ አነጋጋሪ ጉዳዪች እየተነሱ ይገኛሉ፡፡
ከእነዚህም መካከል የፕሬዝዳታዊ ምርጫ እጩዎች እና የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት እጩዎች ግንባር ቀደሙን ይይዛል ፡፡ አሁን ካሉት የፌዴሬሽን አመራሮች መካከል አቶ ጁነዲን ባሻ ጨምሮ አቶ ተክለይኒ አሰፋ አበበ ገላጋይን እንዲሁም አቶ አሊ ሚራ ለፕሬዝደነትነት እና ለስራ አስፈጻሚነት በዚሕኛውም ምርጫ ለመወዳደር መሰናዳታቸው ተሰምቷል፡፡
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ከ31 አመታት በኋላ የተሳትፎ ትኬቷን ስትቆርጥ የብሄራዊ ቡድኑ ዋና አሰልጣኝ የነበሩት አቶ ሰውነት ቢሻው ለስራ አስፈጻሚነት እንዲሁም በወቅቱ ፌዴሬሽኑ አመራር ቦታ ላይ የነበሩት አቶ ተካ አስፋው አማራ ክልልን ወክለው ለፌዴሬሽኑ ፕሬዝደንትነት በዘንድሮ ምርጫ እንደሚሳተፉ እርግጥ ሆኗል፡፡
የአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የቀድሞውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ዮሀንስ ሰሃሌን ለፕሬዝደንትነት እጩ አድርጎ ሲያቀርብ በዘንድሮ የአዲስ አበባ ሲቲ ካፕ ላይ ተመስጋኝ ስራ ከሰሩ የአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አመራሮች መካከል ኢ/ር ሃ/ኢየሱስ ፍሰሐን ለስራ አስፈጻሚ ኮሜቲ አባልነት ይመጥኑኛል ሲል በእጩነት ማቅረቡ ተሰምቷል፡፡
ለቅዱስ ጊዮርጊስ እና ለኢትዮጵያ ቡና ተጫውቶ ያለፈው አንተንህ ፈለቀ በኦሮሚያ ክልል ለፕሬዝደንትነት ይመጥናል ተብሎ በእጩነት ሲቀርብ የኦሎምፒክ ኮሚቴ ዋና ፀሀፊ ታምራት በቀለን ደግሞ ለስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ እጩ ውስጥ መካተቱ ከወዲሁ እየተነገረ ይገኛል፡፡
ከወዲሁ በርካቶችን ያነጋገረው እና እውነት ይሆን እንዴ ተብሎ የተጠየቀው ደግሞ የቀድሞ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝደንት የሆኑት ዶክተር አሸብር ወልደ ጊዮርጊስ ደቡብ ክልልን በመወከል ለፕሬዝዳንትነት መታጨታቸው ተሰምቷል፡፡ ዶክተሩ ከዚህ ቀደም ፌዴሬሽኑን የመሩ እና በበርካቶች የተተቹ ስልጣኔ ተቀማ በማለት ለፊፋ አቤት ያሉ በዚህም ኢትዮጵያን ለ2 አመታት ከማንኛውም እግር ኳስ ውድድር ያስቀጡ መሆኑ ይታወሳል፡፡
በጠቅላላ ጉባኤ የሚወዳደሩ ሁሉም ተወዳዳሪዎች እሰከ ጥቅምት 15 ድረስ በፌዴሬሽኑ ጽህፈት ቤት በሚወክሏቸው ክልሎች ስማቸው የሚተላለፍ ሲሆን ለፕሬዝዳንትነት ከወዲሁ 6 ሰዎች ምን አልባት በጠቅላላ ጉባኤው ኮታው 10 ወደ 7 ይቀንሳል ተብሎ በሚጠበቀው ለስራ አስፈጻሚነት ቦታ ደግሞ 11 ሰዎች እስካሁን ባለው ሂደት ከወዲሁ መታጨታቸው እርግጥ ሆኗል፡፡